የእግዚአብሔር ተስፋ እና የክርስቶስ መንግሥት
ዋናው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል - 2 ሳሙ 7:8–16
ዋናው ጭብጥ
እግዚአብሔር ለዳዊት የዘላለም ዙፋን እንደሚሰጠው ተስፋ ገባለት፤ ያም ተስፋ የዳዊት ልጅና የዘላለም ንጉሥ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ተፈጸመ የሚል ነው።
መግቢያ
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉት ታላላቅ እውነቶች አንዱ እግዚአብሔር የተናገረውን ተስፋ እንደሚጠብቅ መነገሩ ነው። በ2 ሳሙ 7 ላይ ዳዊት ለእግዚአብሔር ቤት (ቤተ መቅደስ) ሊሠራለት ፈለገ፤ እግዚአብሔር ግን ለዳዊት "ቤት" (ዘር/መንግሥት) እንደሚሠራለት ነገረው። ይህ ቤት ከድንጋይ የሚሠራ ሕንፃ ሳይሆን ለዘላለም የሚኖር መንግሥት ነበር። ይህ ተስፋ ከዳዊትና ከሰሎሞን አልፎ፣ መንግሥቱ ወደማያልቀው ወደ እውነተኛው ንጉሥ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያመለክት ነው።
1. የእግዚአብሔር ጸጋ ከእኛ ዕቅድ ይቀድማል
ዳዊት በቤተ መንግሥት ይኖር ነበር፤ የእግዚአብሔር ታቦት ግን አሁንም በድንኳን ውስጥ ነበረ። ዳዊት ይህ ትክክል እንዳልሆነ ስለተሰማው ለእግዚአብሔር ቤት ለመሥራት አቀደ። ነገር ግን እግዚአብሔር የዳዊትን ዕቅድ አቆመውና ዳዊት ያለው ነገር ሁሉ ከእግዚአብሔር ጸጋ የመጣ መሆኑን አስታወሰው። እግዚአብሔር እንዲህ አለው፦ "ከበግ ጥበቃ ወሰድኩህ፣ በሄድክበት ሁሉ ከአንተ ጋር ነበርኩ፣ በጠላቶችህም ላይ ድልን ሰጠሁህ።" ይህ ለእኛ ትልቅ ትምህርት ነው፦ ለእግዚአብሔር ምንም ነገር ከማድረጋችን በፊት፣ እግዚአብሔር ለእኛ ያደረገውን ማሰብ አለብን። ዳዊት ለእግዚአብሔር የሆነ ነገር መስጠት ፈለገ፤ እግዚአብሔር ግን አስቀድሞ ለዳዊት ሁሉንም ነገር ሰጥቶት ነበር። በወንጌል ውስጥ ያለው እውነትም ይኸው ነው። የምንጀምረው በሥራችን ሳይሆን በእግዚአብሔር ጸጋ ነው። ድነት (ድኅነት) እኛ ለእግዚአብሔር የምንገነባው ነገር አይደለም፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ በኩል ለእኛ የገነባውና እንጂ።
የአዲስ ኪዳን ጥቅሶች፦
• ኤፌሶን 2:8–9 — የዳናችሁት በጸጋ በ እምነት ነው፤ ይህ ከእናንተ አይደለም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ።
• ዮሐንስ 15:16 — "እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም።"
2. እግዚአብሔር ለዳዊት የዘላለም መንግሥት ተስፋ ሰጠው
እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር ቃል ኪዳን ገባ፤ "ቤቱ"፣ "መንግሥቱ" እና "ዙፋኑ" ለዘላለም እንደሚጸኑ ተስፋ ሰጠው። ይህ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ካሉ እጅግ ጠቃሚ ተስፋዎች አንዱ ነው። ይህ ተስፋ ከሰሎሞን፣ ከማንኛውም ምድራዊ ሥርወ-መንግሥት እና ከእስራኤል የፖለቲካ ታሪክ በላይ የላቀ ነው።
መጀመሪያ ላይ ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን ስለሠራና ከዳዊት በኋላ ስለነገሠ የተስፋው ፍጻሜ እርሱ ይመስል ነበር። ነገር ግን የሰሎሞን መንግሥት ለዘላለም ስላልቆየ የመጨረሻው ፍጻሜ እርሱ አልነበረም። "ለዘላለም" እና "ለዘላለም የጸና" የሚሉት ቃላት የሚያሳዩት እግዚአብሔር ከሰሎሞንና ከዳዊት ስለሚበልጥ ንጉሥ ተስፋ እንደሰጠ ነው። ይህ ተስፋ የእግዚአብሔር ሕዝቦች በታሪክ ውስጥ በገጠሟቸው ተስፋ መቁረጦችና፣ ስደቶች ውስጥ ጥበቃና ተስፋ ሆኖላቸዋል። ዙፋኑ ባዶ በታየበት ወቅት እንኳ እግዚአብሔር ቃሉን አልረሳም ነበር። ቃል ኪዳኑ ሕያው ነበር፣ ንጉሡም ይመጣ ነበር።
የአዲስ ኪዳን ጥቅሶች፦
• ሉቃስ 1:32–33 — ጌታ አምላክ "የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል... ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም።"
• ዕብራውያን 1:8 — ስለ ልጁ ግን፦ "አምላክ ሆይ፥ ዙፋንህ እስከ ዘላለም ድረስ ይኖራል" ይላል።
3. ኢየሱስ የተስፋው የዳዊት ልጅ ነው
አዲስ ኪዳን የ2 ሳሙ 7ን ትርጉም ግልጽ ያደርገዋል፦ ኢየሱስ እግዚአብሔር ከዳዊት ጋር የገባው ቃል ኪዳን ፍጻሜ ነው። እርሱ ከዳዊት ዘር ተወለደ፣ የዳዊት ልጅ ተብሎ ታወጀ፣ ከሙታን ተነሳ፣ በእግዚአብሔርም ቀኝ ከበረ። መልአኩ ለማርያም ሲናገር ኢየሱስ በአባቱ በዳዊት ዙፋን ላይ እንደሚቀመጥና ለዘላለም እንደሚነግሥ ተናግሯል። ይህም ቀጥተኛ የቃል ኪዳን ቋንቋ ነው። ጴጥሮስም በጰንጠቆስጤ ዕለት እግዚአብሔር ከዘሩ አንዱን በዙፋኑ ላይ እንደሚያስቀምጥ ለዳዊት ተስፋ እንደሰጠውና ያም ንጉሥ ኢየሱስ እንደሆነ መሰከረ። ሐዋርያው ጳውሎስም ወንጌል ስለ ልጁ እንደሆነና ይህም ልጅ "በሥጋ ከዳዊት ዘር" እንደተወለደ ተናግሯል። በሌላ አነጋገር ኢየሱስ መንፈሳዊ መሪ ወይም የሥነ-ምግባር መምህር ብቻ አይደለም፤ እርሱ እግዚአብሔር ከብዙ ዘመናት በፊት ተስፋ የሰጠው የቃል ኪዳን ንጉሥ ነው። ትንሣኤውም ይህንን ያረጋግጣል። ኢየሱስ ከዳዊት ዘር መምጣት ብቻ ሳይሆን፣ ሞትን ድል አድርጎ አሁን በሥልጣን ይነግሣል። የዳዊት ዙፋን ፍጻሜ ያገኘው በጊዜያዊ ምድራዊ መንግሥት ሳይሆን በዘላለማዊው የክርስቶስ አገዛዝ ነው።
የአዲስ ኪዳን ጥቅሶች፦
• ሮሜ 1:3–4 — በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ተወለደ... በትንሣኤው የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑ በኃይል ተገለጠ።
• ሐዋ ሥራ 2:30–36 — እግዚአብሔር ኢየሱስን በማስነሳትና ጌታም ክርስቶስም በማድረግ ተስፋውን ፈጸመ።
• 2 ጢሞ 2:8 — "ከሙታን የተነሳውን፣ ከዳዊት ዘር የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን አስብ።"
ተግባራዊ ተዛምዶ
የ2 ሳሙ ምዕራፍ 7 ፍጻሜው የዘገየ ቢመስልም በእግዚአብሔር ተስፋዎች እንድንታመን ያስተምረናል። ዳዊት ሙሉውን ስዕል አላየም ነበር፤ ነገር ግን እግዚአብሔር የክርስቶስን መምጣት እያዘጋጀ ነበር። ይህም ማለት የእግዚአብሔር ተስፋዎች የዘገዩ ቢመስሉም የእርሱ ጊዜ ፍጹም ስለሆነ ልንታመነው እንችላለን።
በተጨማሪም ተስፋችንን የት ላይ ማድረግ እንዳለብን ያስተምረናል። የመጨረሻ ተስፋችንን በሰዋዊ መሪዎች፣ በምድራዊ መንግሥታት ወይም በጊዜያዊ ስኬት ላይ አናደርግም። ተስፋችን አገዛዙ በማይናወጠው በዘላለማዊው ንጉሥ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ነው።
ይህም ለንግሥናው እንድንገዛ ይጠራናል። ኢየሱስ የተስፋው የዳዊት ልጅ ከሆነ፣ እርሱ መድኃኒት ብቻ ሳይሆን ጌታም ነው። በፊቱ እንድንሰግድ፣ በእርሱ እንድናምንና በእርሱ አገዛዝ ሥር እንድንኖር ተጋብዘናል።
ማጠቃለያ
ዳዊት ለእግዚአብሔር ቤት ሊሠራ ፈለገ፤ እግዚአብሔር ግን ለዳዊት ቤት እንደሚሠራለት ተስፋ ገባ። ያ ቃል ኪዳን ስለ እስራኤል ያለፈ ታሪክ ብቻ ሳይሆን ስለሚመጣው የክርስቶስ መንግሥት ነበር። ኢየሱስ እውነተኛው የዳዊት ልጅ፣ የዘላለም ንጉሥና የእግዚአብሔር ተስፋ ፍጻሜ ነው።ስለዚህ የ2 ሳሙኤ 7 መልዕክት ይህ ነው፦ እግዚአብሔር ቃሉን ይጠብቃል፣ ቃሉም በኢየሱስ ክርስቶስ ተፈጽሟል። ዙፋኑ ባዶ አይደለም፤ ንጉሡ መጥቷል። መንግሥቱም አያልቅም።
Source: https://cmaeec.com/w...
John 3:16
Whoever believes in him shall not perish but have eternal life.